Thursday, December 20, 2012

መሪዎቻችን ዳግም የስቃይ ቤርሙዳ ውስጥ

መሪዎቻችን ዳግም የስቃይ ቤርሙዳ ውስጥ

መሪዎቻችን ላይ በማዕከላዊ ሲፈጸም የነበረው ቶርች ቃሊቲ ውስጥ በአዲስ ስልት ተጀምሯል፡፡ በአገሪቱ ሕግ የሚገዛው የፍትህ አካል ለአይን እንኳ እየጠፋ ነው፡፡

ዘግይቶ በደረሰን መረጃ ያለምንም መረጃ ከሕግ አግባብ ውጪ በግፍ ባፈጸሙት ወንጀል በሀሰት ተከሰው በማዕከላዊ ወህኒ ቤት ግፍና በደል ሲፈጸምባቸው የቆዩት መሪዎቻችን እና ወንድሞቻችን በቃሊቲ ማረሚያ ቤትም ዘግናኝ ግፎችን ማስተናገድ መጀመራቸውን አረጋግጠናል፡፡ በተወሰኑ የቃሊቲ ማረሚያ ቤት ዞኖች ውስጥ ያሉ መሪዎቻችንና ወንድሞቻችን በሚያሳፍር መልኩ ራሳቸውን መቆጣጠር ከማይችሉና አእምሮአቸውን ከሳቱ የአእምሮ ህሙማን ጋር በጋራ እንዲታሰሩና መኝታ እንዲጋሩ መደረጋቸው ታውቋል፡፡ ይህ የመንግስት ስልት ከዚህ ቀደምም በቃሊቲና በሌሎች ወህኒዎች ሲሰራበት የቆየ መሆኑ የሚታወቅ ሲሆን የታሳሪዎችን ህይወት አደጋ ውስጥ በመክተት በማንኛውም አጋጣሚ አደጋ ሊያደርስ ከሚችል የአእምሮ እመምተኛ ጋር መኝታ ማጋራትና መዘዙን መሪዎቻችን እንዲሸከሙት የማድረግ ስልት ተግባራዊ በመደረግ ላይ ይገኛል፡፡
በግልጽ እንደሚታወቀውም የአእምሮ ህሙማን እስረኞች በማረሚያ ቤቱ ሐላፊዎችና በደህንነቶች የተለያዩ ጥቅማ ጥቅሞች እየተገቡላቸው አንድ አንድ አስቀያሚ ድርጊቶችን ሐላፊዎቹ በሚፈልጉት እስረኛ ላይ እንዲፈጽሙ ይደረጋል፡፡ ይህም ማለት መሪዎቻችን ባላሰቡትና ባልተዘጋጁበት መልኩ ከጎናቸው ካለው ታሳሪ ድብደባ ወይም ሌላ የከፋ ተግባር ሊደርስባቸው እንደሚችልና ህይወታቸውንም የከፋ ችግር ውስጥ ሊከተው እንደሚችል ስጋት አለ፡፡ ደብዳቢውም ሆነ ሌላ የከፋ ጉዳት አድራሹ የአእምሮ ህመምተኛ በመሆኑም በሰራው ወንጀል ሊጠየቅ የሚችልበት አግባብ የለም፡፡ ብዙዎቹ የአእምሮ ህሙማን ደብዳቢዎች የታዘዙትን ከሰሩ አመክሮ (ከተፈረደባቸው ወቅት ቀድመው እንዲለቀቁ) ይሰጣቸዋል፡፡ ሌሎች ማበረታቻዎችም ከሀላፊዎቹ ይሰጧቸዋል፡፡ አሁን የእኛ መሪዎች ላይ አደጋ እንዲያደርሱ ተልእኮ የተሰጣቸው የአእምሮ ህሙማን መሪዎቻችን ላይ ያሻቸውን አደጋ ለማድረስ በማወቅም ሆነ ባለማወቅ አሳቻ ጊዜ እየጠበቁ ለመሆኑ ምንም ጥርጥር የለውም፡፡ ምልክቶችም በግልጽ እየታዩ ነው፡፡

መሪዎቻችን እና ወንድሞቻችንን አቅላቸውን ከሳቱ ህመምተኞች ጋር ከማጎር ባለፈ፣ ቤተሰቦቻቸውንና ሌሎች ሕጉ የሚፈቅድላቸውን ሰዎች የማግኘት መብታቸው ከማእከላዊ ወህኒ ቤት ጀምሮ ሲነፈጉ መቆየታቸው የሚታወቅ ሲሆን ፍ/ቤት በቀረቡባቸው አጋጣሚዎች ማረሚያ ቤቱንና የሚደርስባቸውን ስቃይና ሲ-ሰብአዊ አያያዝ በተደጋጋሚ ቢያሳውቁም መፍትሄ ሳያገኙ ቀርተዋል፡፡ መሪዎቻችን በቃሊቲ ከደረሱባቸው አሰቃቂ ድርጊቶች በኋላ አሁን በቃሊቲ ከማንም እስረኛ ጋር እንዳይገናኙ፣ ምንም አይነት ንግግር እንዳያደርጉ፣ ይህንን የሚያደርጉ ታሳሪዎች ካሉም ቅጣት እንደሚጣልባቸው በመገለጹ ታሳሪዎች ወንድሞቻችንን እንዲሸሿቸው እየተገደዱ ነው፡፡ በዚህም ለከፍተኛ ማህበራዊ መገለልና ብቸኝነት ተዳርገዋል፡፡ (በዚህ ጉዳይ ላይ ተጨማሪ መረጃዎችን የምናወጣ መሆኑን እንገልጻለን) ከዚህም አልፎ ግን ሰላማቸውን እንዲያጡና እረፍት እንዳያገኙ በዚህም ተስፋ ለማስቆረጥ ብሎም ራሳቸውም ህመምተኛ እንዲሆኑ ለማድረግ ከፍተኛ ጥረት እየተደረገ ይገኛል፡፡ መሪዎቻችን አሁን በቃሊቲ ማረሚያ ቤት ውስጥ በተናጥል የማስፈራሪያ፣ የዛቻ፣ የማንቋሸሽ አሳፋሪ ድርጊቶች በማረሚያ ቤቱ ሐላፊዎችና ይህ ተልእኮ በተሰጣቸው ግልሰቦች እየተፈጸመባቸው መሆኑ ታውቋል፡፡ ትንኮሳውም ከተለያዩ አቅጣጫዎች እንደበረታባቸው ለማወቅ ተችሏል፡፡

የማረሚያ ቤት ሐላፊዎችም ሆኑ የደህንነት አባላት ከቅርብ ግዚያት ወዲህ በዚህ አይነት ተግባራት መልሰው መዘፈቅ የጀመሩት የመሪዎቻችን ንጹህነትና የአላማ ጽናት ሰላማቸውን ስለነሳው መሆኑ ምንም ጥያቄ የለውም፡፡ እንዲሁም መሪዎቻችንና ሌሎች ታሳሪ ወንድሞቻችን እየተቀዳጁ ያሉት ሕዝባዊ ክብር ከቀን ወደ ቀን እየጨመረ መምጣቱ፣ እነሱን ነጻ ለማውጣት ሕዝባችን እየከፈለ ያለው ይህ ቀረሽ የማይባል መስዋእትነት በማሻቀቡ፣ ያገኙት አለም አቀፋዊ ተቀባይነትና ተሰሚነት ሞራላዊ ልእልናቸውን ከፍ ያደረገው በመሆኑና በአላማቸውም መጽናታቸው ከምንም በላይ ወንጀለኞች አለመሆናቸው በሁሉም ዘንድ ግልጽ እያለ መምጣቱ የእግር እሳት የሆነባቸው በክፋት የተወጠሩ የማረሚያ ቤት አስተዳደሮችና ደሀንነቶች በትእግስት የሚያልፉት አልሆነላቸውም፡፡ ለዚህም ተስፋ ማስቆረጥንና አእምሮአዊ ሰላም መንሳትን አላማ በማድረግ ዳግም የጭቃ ጅራፋውን እያጮሁ ነው፡፡

የኢትዮጵያ ሕገ መንግስት የሰው ልጆች ላይ ኢ-ሰብአዊ አያያዝ መከልከሉን አስመልክቶ በአንቀጽ 18 ንኡስ አንቀጽ 1 ‹‹ማንኛውም ሰው ጭካኔ ከተሞላበት፣ ኢሰብዓዊ ከሆነ ወይም ክብሩን ከሚያዋርድ አያያዝ ወይም ቅጣት የመጠበቅ መብት አለው ይላል፡፡›› ሕገ መንግስቱ በአንቀጽ 21 ‹‹በጥበቃ ሥር ያሉና በፍርድ የታሰሩ ሰዎች መብት›› በሚለው ርዕስ ስር በንኡስ አንቀጽ 1 ‹‹በጥበቃ ሥር ያሉና በፍርድ የታሰሩ ሰዎች ሰብዓዊ ክብራቸውን በሚጠብቁ ሁኔታዎች የመያዝ መብት አላቸው፡፡›› በንኡስ አንቀጽ 2 ደግሞ ‹‹ከትዳር ጓደኞቻቸው፣ ከቅርብ ዘመዶቻቸው፣ ከጓደኞቻቸው፣ ከሃይማኖት አማካሪዎቻቸው፣ ከሐኪሞቻቸው እና ከሕግ አማካሪዎቸው ጋር ለመገናኘትና እንዲጐበቿቸውም ዕድል የማግኘት መብት አላቸው፡፡›› በሚል ግልጽ ድምዳሜውን አስቀምጧል፡፡ ለመሆኑ ሕግ የማይገዛቸው የማረሚያ ቤት ሀላፊዎችና የደህንነት አባላት ይህን ሕግ ለአፍታም ያህል ለማክበርና ለማስከበር ለምን ፍላጎት አይኖራቸውም፡፡ ይህን ሕገ መንግስታዊና አለም አቀፋዊ ድንጋጌ ‹‹እናስጠብቃለን›› የሚሉት የፍትህ እና የሰብአዊ መብት ተቋማት የት ናቸው፡፡? ሕገ መንግስቱ እስከመቼ ነው የሚጣሰው? እስከመቼስ ነው የጥቂት ግለሰቦች መቀለጃ እና ፍትህ መንሻ የሚሆነው? እኮ እስከ መቼ?

No comments:

Post a Comment