ጁመዓ የማይቀርበት ታሪካዊ ቀጠሮ አለን!የኢስላም አስተምህሮ ከኛ ይደርስ ዘንድ የታለፈባቸው ወሳኝ መንገዶች እኛም እንድንጓዝባቸው የአላህ ፍላጎት መሆኑን እነሆ ተጨባጩ ያስረዳል፡፡ አያት ቅድመ አያቶቻችን ዲናቸውን በመጠበቅ የሰሩት አኩሪ ገድል በእኛም እንዲደገም ወቅቱ እየተጣራ ነው፡፡ የወቅቱንም ጥሪ በተግባር የሚመልሱ ሚሊዮን ቢላሎችና ሚሊዮን ሱመያዎችን በእርግጥም አይተናል፡፡ የቢላልና የሱመያን መንገድ ለመረጃ ፍጆታነት ሳይሆን ለህይወት መርህነት የሚጠቀሙ ኢትዮጵያውያኖችን አይናችን አይቷል፡፡ ታሪካችንም ዘግቦት እያለፈ ነው፡፡ ይህን በውስጣችን እያለ ሳናጤነው የኖርነው ትልቅ የአላህ ኒዕማን በገሃድ እንዲታይ ያደረገው ደግሞ ከአመታት በፊት በመንግስት ተመርጦልን ከ365 ቀናት በፊት ልንጠመቀው የተዘጋጀልን ‹‹ሙስሊሞችን ዳግም የማስለም›› ሃገራዊ ዘመቻ ነው፡፡ ይህንኑ ዘመቻ የሚመራው ደግሞ የመንግስትን ትከሻ ተደግፎ በመጅሊስ ስም የተሰባሰበው የካድሬዎች ቡድን ነው፡፡ የነዚህ የጥፋት ተልዕኮ ያነገቡ ሁለት ሃይሎች የመጀመሪያ ሰለባ የነበረው ደግሞ ከነስያሜያቸው አፄ እና ወታደራዊ በመባል የሚታወቁ ሁለት መንግስታትን አሳልፎ ዴሞክራሲያዊ በሚል ስም በተሰየመው መንግስት ላይ የደረሰው የአወሊያ ተቋም ነው፡፡ የ365 ቀናት ጉዟችንም ከነዚህ ሶስት ነጥቦች ጋር የተያያዘ ነው፡፡ ሶስቱ ነጥቦችም የነገሩ መነሻ እንዲሆኑ ያስቻለው ትልቁ ነጥብ ግን መንግስት ሃገር የሚተዳደርበትን ህገመንግስት በማንአለብኝነት በአደባባይ ደግሞ ደጋግሞ መጣሱ ነው፡፡

